የውጭ አካላት የፈለጉትን ቢሉም በኢትዮጵያ ጉዳይ ወሳኝ አይሆኑም ሲሉ የምክር ቤት አባላት ገለፁ

የተለያዩ የውጭ አካላት የፈለጉትን አስተያየት ቢሰጡም በኢትዮጵያ ጉዳይ ከዜጎቿ በላይ ወሳኝ ሊሆኑ እንደማይችሉ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለፁ።
የአገር ኅልውናና ሉኣላዊነት ላይ የተደቀነውን አደጋ ለመከላከል መተግበር ለጀመረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስኬታማነት የበኩላቸውን እንደሚወጡ በመጥቀስም መላው ሕዝብ ለአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ተፈጻሚነት ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።
የምክር ቤቱ አባል እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በኢትዮጵያ ላይ የተከፈቱ የወታደራዊ፣ የምጣኔ ሃብትና የፕሮፓጋንዳ ጦርነቶች የአገር ኅልውናን እንደሚፈታተኑ ገልጸዋል።
እነዚህ ኃይሎች ከሌሎች የኢትዮጵያ ጠላቶች ጋር ተሻርከው በውግንና እየሰሩ ያለውን ተግባር ለመቀልበስ የጸደቀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ያለውን ፋይዳም ገልጸዋል።
ሌላኛው የምክር ቤት አባል ክርስቲያን ታደለ የተለያዩ አካላት የፈለጉትን አስተያየት ቢሰጡም በኢትዮጵያ ጉዳይ ከዜጎቿ በላይ ወሳኝ ሊሆኑ እንደማይችሉ ተናግረዋል።
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈፃፀም መርማሪ ቦርድ አባል የሆኑት ክርስቲያን ቀደም ሲል በነበሩ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጆች የመርማሪ ቦርድ አባል ስብጥር የፓርቲ ማዕከላዊነት ይንጸባረቅበት እንደነበረ አስታውሰዋል።
የተሰጣቸውን ኃላፊነት በነጻነት በመከወን ለአዋጁ ተፈጻሚነት የበኩላቸውን እንደሚወጡም አረጋግጠዋል።
የምክር ቤቱ አባላት ኢትዮጵያዊያን በአገራቸው አንድነትና ኅልውና ላይ አደጋ የደቀነውን የሽብር ቡድን ለመደምሰስ እያደረጉ ያለውን ተጋድሎ እንዲያጠናክሩም ጠይቀዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።
ተጨማሪ ያንብቡ:  128 ኛውን የዓደዋ  ድልን ስናከብር ይኽንን ታሪክ ማወቅ አለብን

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share